Daniel Kibret
631 posts

Daniel Kibret
@danielkibret
Advisor Minister on social affairs, the Prime Minister of Ethiopia - @PMEthiopia ; Member of Ethiopian Parliament; Author of 35 books.
Addis Ababa, Ethiopia Beigetreten Eylül 2011
147 Folgt352.1K Follower

የአውግቸው ተረፈን “ወይ አዲስ አበባ” ሳነብ አንድ የሚያስቀኝ ክፍል አለ፡፡ ከጎጃም ገጠር የመጣው አውግቸው አንድ ቀን አራዳ ሲዘዋወር “አንድ ረዥም ሕንጻ” ያያል፡፡ እዚያ ሕንጻ ሥር ቆሞ ሽቅብ ሲያየው፣ ሕንጻው “ዘመም እያለ ወጥቶ” ሊወድቅ የደረሰ ይመስለዋል፡፡ ከዚያ “ወግድ ሊወድቅ ነው” እያለ ሩጫውን ተያያዘው፡፡ ሩጦ ሩጦ ከደከመው በኋላ ነበር ሕንጻው እንዳልዘመመና እንደማይወድቅ የገባው፡፡ ለካስ ሊወድቅ የደረሰው በረሃብ የተሰቃየው ራሱ አውግቸው ነበረ፡፡
አንዳንዴ ዋሽንግተን ፓርኪንግ ሎት ውስጥ ተቀምጠው “መንግሥት ሊወድቅ ነው” የሚሉትን ሰዎች ስሰማ አውግቸው ተረፈ ትዝ ይለኛል፡፡
ከሥር ሆኖ፣ ቀና ብሎ ማየት፣ እንዴት ከባድ ነገር ነው፡፡ ራስ ያዞራል።

AM

ጎሉን ለጀግናው ተውለት
በተመልካቹ፣ በደጋፊው ወይም ኳሱን ባቀበለው ሰው ስም ጎል አይመዘገብም። የሚመዘገበው መጨረሻ ላይ አጠናቆ ጎሉን ባስገባው አጥቂ ስም ነው።
ሌሎች በጨዋታው ላይ ለነበራቸው አበርክቶ ይደነቃሉ፤ ይመሰገናሉ፤ የኮከብ ተጨዋችም፣ የጠባይም፣ የኮከብ አቀባይም ሽልማት ይወስዳሉ።
የጨዋታው ውጤት በዋናነት የሚወሰነው በጎሉ ነው። ምርጥ አርገህ ብትጫወትም ጨርሰህ ካላስገባህ ውጤትም ዋንጫም የለህም።
ደስታን ለደጋፊው፣
ርካታን ለተጨዋቾቹ
ጎሉን ለጀግናው ተውለት።
ጎል የሚጠራው በአግቢው ነውና

AM

ሞዐ ተዋሕዶ የፖለቲካ እንጂ የሃይማኖት ተቋም አልነበረም። ሽፋኑ ግን ሃይማኖት ነው። ያቋቋሙትም በቤተ ክህነት ውስጥ ያሉ፤ በአንዳንድ ማኅበራት ውስጥ ያሉና በፖለቲካው ውስጥ ያሉ አካላት በመቀናጀት ነው።
ከሰባቱ አመራሮች ሁለቱ ውጭ ሄደዋል። ሁለቱ አሁንም የአንድ ማኅበር አመራሮች ናቸው። አንዱ የጃውሳ የንስሐ አባት ሆኖ ከፍኖተ ሰላም ጠፍቷል። የጃውሳ ሰዎች ትልልቅ መስቀል ማንገት የጀመሩት በእርሱ ምክር ነው። አንዱ በሌላ ወንጀል ታሥሯል። አንደኛው የአብነት መምህር ነኝ ብለው ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ አድፍጠዋል።
ዛሬ መሥራቾቹ የሚናገሩት ከፊል እውነቱን ነው። ገና ወደፊት እውነቱ ጥርሱን ያገጣል።
ሞዓ እንደተመሠረተ በማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቭዥን እንዲቀርብ ለምን ተደረገ? ቦሌ በሚገኝ ሆቴል እንዲሰበሰብ ማን ነበር የፈቀደለት? በቤተ ክህነቱ ሆነው ድጋፍ ሲያደርጉለት የነበሩ ሰዎች እንዴት ካሊፎርኒያ እና ደቡብ አፍሪካ ሀገረ ስብከት ተሾሙ? ከቤተ ክህነቱ ሰዎች ሰሜን ጎጃምንና ባሕርዳርን ለሞዓ መፈንጫ እንዲሆን የፈቀደው ማን ነበር? ከኋላ ሆኖ ሲያደራጅ የነበረው "ሰባኪ" ዛሬም አሜሪካ እየዞረ በአንድ የንግድ ቴሌቭዥን ስም ገንዘብ የሚሰበስበው ለምንድን ነው?
ስለ ሞዓ መናገር የጀመሩት ሰውዬ ሲበሳጩ ሲበሳጩ ይነግሩን ይሆናል።

AM

በሁሉም ነገር ተሸንፎ ከሊግ መውረዱን ያረጋገጠ አንዳንድ ቡድን፣ የመጨረሻውን ጨዋታ የሚያደርገው በአጫዋቹ ተገዶ ብቻ ነው። ለዋንጫ ስለማይጫወት ለእርግጫ ይጫወታል። ዓላማ ስለሌለው ዒላማም የለውም። ቢያገባም ባያገባም ለውጥ ስለሌለው ኳሱን ወዳገኘውና እንዳገኘው ይጠልዛል። አንዳንዴም ወደ ተጋጣሚው ቡድን ሳይሆን ወደ ሕዝቡ ኳሱን ይመታል። ተመልካቹ ለምን? ብሎ ሲቃወመው ደግሞ ይሳደባል፣ አልፎም ብጥብጥ ያስነሣል። ቢጫ ቢያይ፣ ቀይ ቢሳለም፤ ተስፋ የቆረጠ ቡድን ጨዋታው የጨበራ ነው። ተጨዋቾቹ የሚበሉት ዋንጫ ስለሌላቸው እርስ በራሳቸው ይበላላሉ።
የጃውሳ ነገር እንደዚህ ሆኗል። እሱ ተሸነፎ ተስፋ ቆርጧል። የሚጫወተው ለአጫዋቾቹ ሲል ነው።
AM

ደመናው አጉረመረመ። እስኪበቃውም ጮኸ።
ፀሐይ ግን ድምጽ የላትም።
ከደመናው ውስጥ መብረቅ ወጣ። አገር ይያዝልኝ አለ።
ፀሐይ ግን ዝም ብላ ሥራዋን ትሠራለች።
ደመናው ፀሐይዋን ሸፈነ። እንደ ጉድ ዝናቡን ጣለ።
ዝናቡ ተጨቃጨቀ፤ ተንጫጫ፣ ተጯጯኸ
ፀሐይም ዝም ብላ ሥራዋን እየሠራች ቆየች።
ዝናቡ አበቃ። ደመናውም ተገፈፈ።
ፀሐይም "የሽሮ ድንፋታ ውኃ እስኪገባበት" ብላ ወጣች።
ጎርፉም ቁልቁል ወረደ።
ፀሐይም ቁልቁል ዝም ብላ አየችው።
ጎርፉም ድራሹ ጠፋ።
ፀሐይም በጨረሯ ተሰናበተችው።
################
እነሆ ዘመኑ በፀሐይ እንጂ በደመና አይቆጠርም።
AM

የዐቢይ ምጽዋተኞች
ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ(በረከታቸው ይደርብንና) በነበሩ ዘመን አንድ ሰው እሳቸውን ሰድቦ መጽሐፍ ያሳትማል፡፡ ቤተ ክህነቱ ይከሰዋል፡፡ እሱም ይታሠራል፡፡ በኋላ አቡነ ጳውሎስ ይሰማሉ፡፡
“ለምን ከሰሳችሁት” አሉ
“እርስዎን ሰድቦ፣ መጽሐፍ አሳትሞ እየሸጠ ነው” ብለው መጽሐፉን አምጥተው አሳዩዋቸው፡፡
“ለመሆኑ ልጁ ሥራ አለው” አሉ
“ኧረ የለውም፤ ይሄንኑ እየሸጠ ነው የሚበላው”
“ሊሸጥ የሚችል ስምስ አለው”
“ኧረ ስሙ መንገድ ላይ ወድቆ ቢገኝ ማንም አያነሣውም”
“በሉ ተውት፤ ከሚርበው ስሜን ሽጦ ይብላ፤ ለእኔም እንደ ምጽዋት ይቆጠርልኛል፤ እሱኮ የሚሠራው ሥራም፣ የሚሸጠው ስምም ስለሌለው ነው” አሉ ይባላል፡፡
አሁን አሁን የዐቢይን ስም ሽጠው የሚበሉ ምጽዋተኞች ብቅ ብቅ ብለዋል፡፡ እነዚህ ሰዎች ሁለት ነገር የላቸውም፡፡ አንድም ሥራ የላቸውም፤ አንድም የሚሸጥ ስም የላቸውም፡፡ ያላቸው አማራጭ የዐቢይን ስም ሸጠው መብላት ነው፡፡ ልጆቻቸውም በዚህ ሽያጭ ነው የሚያድጉት፤ ቢልም የሚከፍሉት ከዚሁ ሽያጭ ነው፡፡ ለዐቢይ በዋናነት የሚጸልዩት እነዚህ ሰዎች ናቸው፡፡ ስሙ እንጀራቸው ነዋ!
እነዚህ የዐቢይ ምጽዋተኞች ናቸው፡፡
ስሙ እንጀራቸው ነው፡፡
ስሙ ልብሳቸው ነው፤
ስሙ የታክሲ ሂሳባቸው ነው፡፡
ያሳደጋቸው የዐቢይ ስም መሆኑን ልጆቻቸውም ያውቃሉ፤ እናም ምኞታቸው አሳዳጊያቸውን ዐቢይን ማየት ነው፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ፡-
ለአንዳንዶች በታላላቅ ፕሮጀክቶች የሥራ ዕድል ተፈጥሮላቸዋል፤
ለአንዳንዶች የውጭ ሀገር የሥራ ዕድል ተመቻችቶላቸዋል፤
ለአንዳንዶች በሪሞት የሚሠሩት ሥራ ተዘጋጅቶላቸዋል፤
ለአንዳንዶች በኮሪደር ልማት የሥራ ዕድል አግኝተዋል፤
ለአንዳንዶች በሌማት ትሩፋት የገቢ ምንጭ ተፈጥሮላቸዋል፤
ለአንዳንዶች በአረንጓዴ ዐሻራ የእንጀራ ገመድ ተዘርግቶላቸዋል፤
ለአንዳንዶች በስንዴና በሩዝ አብዮት ሀብት ተትረፍርፎላቸዋል፤
ለአንዳንዶች ቤት ተሠርቶላቸው ሱቅ ተሰጥቷቸዋል፤
ለነ እንቶኔ ደግሞ ስሙን ሸጠው የመተዳደር የሥራ ዕድል ተፈጥሮላቸዋል፤
እናም፤ ምጽዋተኞችን ተዋቸው፤ እዘኑላቸው፤ አትፍረዱባቸው፡፡
ስም በመሸጥ የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው “የዐቢይ ምጽዋተኞች” ናቸው፡፡
AM

(ክፍል ሁለት)
እንደ ደረስኩ የማውቃቸውን ሰዎች መጠየቅ ጀመርኩ። ስሙን የሚሰሙት ሰዎች ሁሉ ይተያዩና ሽፍንፍን አርገው ያልፉታል። አንዳንዶችም " ታውቀዋለህ እንዴ?" ይሉኛል።
አንድ ሰው ብቻ "ለምን ፈለግከው?" አለኝ።
"ቤተሰቦቹ አደራ ብለውኝ" አልኩት።
"ግንኮ ለአንተ ጥሩ አይደለም"አለኝ።
"እንዴት"
"እንጃ፣ ብቻ" ጀምሮ ተወው።
ግራ ገባኝ።
በስንት መከራ ያለበት ወስዶ ሊያገናኘኝ ፈቃደኛ ሆነ።
ያገኘሁት ሱሰኞች የሚያገግሙበት ቦታ ነው። ከዚያ መውጣት አይፈቀድለትም። የሚወስደው መርፌ አለው። አስቀድሞ በማስፈቀድ ብቻ እሱን ገብቶ ማየት ይቻላል። ያውም እሱ ከፈቀደ። ብዙ ጊዜ ሰዎች እንዲያዩት አይፈልግም።
ሳገኘው፣ እጆቹ ይንቀጠቀጣሉ። ፊቱን ፂም ወርሶታል። ዓይኑ መንኗል፡፡ ጆሮ ወድቋል፡፡ ፀጉሩ የቀድሞዋን ካዛንቺስ መስሏል፡፡ ሱሪው ወገቡ ላይ በሁለት ዙር ታሥሯል።
ያ መንደሩ እንደ ማንዴላና እንደ ማኅተመ ጋንዲ፣ በነጻ አውጪነት፤ እንደ ስፓይደር ማን እና ሱፐር ማን፣ በተአምር ሠሪነት የሚተርክለት “ጀግና”፣ ይሄው ከፊቴ እጁ እየተንቀጠቀጠ ቆሟል፡፡
እጁን ለሰላምታ ሰደደው። ቅዝቃዜው ከፍሪጅ የወጣ ይመስላል።
ይህ የማየው ሰው ገጸ ባህርይ ነው። ብዙ ነገሮችን የተሸከመ ገጸ ባህርይ። እንዲሆን የሚጠበቀውና የሆነው ያልተገናኘለት ገጸ ባህርይ። ሰዎች በእማሬ ያጡትን ያሸከሙት - ፍካሬ ነው። መንደሩን ከድህነት ነጻ ያወጣል የተባለው “ጀግና” ራሱን ከሱስ ነጻ ማውጣት አቅቶት ይሄው ይንገዳገዳል፡፡
ማን እንደላከኝ፣ ለምን እንደመጣሁ፣ ጠየቀኝ፡፡ አፉ እየተሣሠረ ብዙ ነገር አወጋኝ፡፡ አሁን አሁን ብዙ ሰዎች እንደማይጠይቁት በተሰበረ ልብ ነገረኝ፡፡ ይህ ሰው - በሩቅ ባሉት ሠፈርተኞች ዘንድ ጀብዱው ይወራለታል፡፡ የቅርቡ ሰዎች ግን ትተውታል፡፡ በስሙ ይነግዳሉ እንጂ እርሱ ተረስቷቸዋል፡፡ እሱ ተረት ሆኗል፡፡
“ምን ትፈልጋለህ” አልኩት በመጨረሻ፡፡
“ወደ ሀገሬ መግባት” አለኝ፡፡
“ዘመዶችህኮ ብዙ ነው የሚጠብቁብህ፤ እንደዚህ መሆንህን አያውቁም” አልኩት፡፡
“እኔም እነርሱም የሚያዋጣን እውነቱን መቀበል ነው” አለ ዓይኖቹን ከተደበቁበት ዋሻ፣ ለጸሎት እንደሚወጣ ግሑስ መሰስ አድርጎ እያወጣቸው፡፡
“ገና ለገና እነርሱ የሚተርኩት ያጣሉ ብዬ ከዚህ በላይ ልሆን አልችልም፡፡ እኔም መስሎኝ ነበር፡፡ እነርሱም መስሏቸው ነበር፡፡ ግን አልሆነም፡፡ ያለሁት እዚህ ነው፡፡ ያውም እነዚህም ከለቀቁኝ ነው” አለ፡፡ ግቢውን በሚንቀጠቀጥ ጣቱ እያመለከተ፡፡
እዚያ ሀገር የነበሩ ጥቂት ደጋግ ሰዎች፤ አዲስ አበባም ያሉ ጥቂት ደጋግ ሰዎች፤ በወቅቱም በሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የነበሩ ሰዎች፤ የአየር መንገድም ሰዎች፣ የሕክምናም ሰዎች ተባብረው ወደ ሀገሩ መለሱት፡፡
በአንድ የአእምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከል ውስጥ እንደነበረ ዐውቃለሁ፡፡
AM

ከ20 ዓመት በፊትይመስለኛል። ከኢትዮጵያ ወደ ውጭ ስሄድ አንድ ቤተሰብ አንድ ሥራ ሰጠኝ። እገሌ የተባለ ሰው ከዚህ ሠፈር እንቶኔ ወደተባለ ሀገር ከሄደ ቆየ። ሲሄድ ለቤተሰቡ፣ ለዘመዱ፣ ለሠፈሩ ብዙ ቃል ገብቶ ነበር። ፈረንጆች ያውቁኛል ስለዚህ ይሄንን ሠፈር ነጻ አወጣዋለሁ ይል ነበር። ሠፈሩም በታላቅ ጉጉት ነበር የጠበቀው።
እንደሄደ የተወሰኑ ዶላሮችና ፎቶዎች ላከ። ሀብታም ሆኗል፤ ሥልጣን ይዟል፣ ነገ ከነገ ወዲያ ይመጣል። የሆኑ ልጆችንም ሊወስድ ነው - ይባላል። የወሰዳቸው ልጆች አሉ ተብሎም ይወራል። በዚህ ሠፈር ታሪኩ ገናና ነው። ከዚያ ሀገር የሚመጣ ሰው የተለያየ ነገር ነው የሚያወራን። ርግጠኛውን ግን ማወቅ አልቻልንም።
አልፎ አልፎ ፎቶው ፌስቡክ ላይ ይወጣል። የአሁን ይሁን የድሮ ፎቶ ማወቅ አልቻልንም። እዚህ ሀገር ገባ፤ እዚህ ቦታ ታየ፤ ይባላል። አሉ ነው ሁሉም።
እስኪ ሄደህ በአካል አግኘው፤ እውነቱን እንወቅ አሉኝ።
እኔም አደራ ተቀብዬ ሄድኩ።
ያገኘሁትን በቀጣይ እነግራችኋለሁ ..
AM




